“በአዲስ ምዕራፍ አዲስ ተስፋ ለትምህርት ውጤታማነት እና ብልፅግና” በሚል መሪ ሲካሄድ የነበረው 28ኛው የአዲስ አበባ ከተማ አቀፍ የትምህርት ጉባኤ ተጠናቋል ።
በትምህርት ጉባኤ ማጠቃለያ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ በባለፈው ዓመት ኢትዮጵያ በበርካታ ጫናዎች ውስጥ ሆና የመማር ማስተማሩ ሂደት ሰላማዊ እና ስኬታማ ሆኖ ማለፉን ገልጸዋል ።
ለዚህ ውጤት ደግሞ መምህራንን ጨምሮ በየደረጃው የሚገኙ የትምህርት ዘርፍ ባለድርሻ አካላት ሚና ከፍተኛ መሆኑን የገለጹት ከንቲባ አዳነች አቤቤ የ2014 የትምህርት ዘመን በስኬት እንዲካሄድ ፣ ሀገር ወዳድ እና ሀገር ገንቢ ትውልድ እንዲፈጠር መምህራን እና የትምህርት ዘርፍ አካላት በትኩረት ሊሰሩ ይገባል ብለዋል ።
አዲሱ ስርአተ ትምህርት በዘንድሮው የትምህርት አመት በተመረጡ ትምህርት ቤቶች በሙከራ ደረጃ ተግባራዊ ይደረጋል ያሉት ከንቲባዋ ስርአተ ትምህርቱ ወደ ሙሉ ትግበራ እንዲገባ የከተማ አስተዳደሩ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን አስረድተዋል።
በዕለቱም በ2013 ዓ.ም የትምህርት ዘመን በስራ አፈፃፀምና በተማሪዎች ውጤት የላቀ አፈፃፀም ያስመዘገቡ ትምህርት ቤቶችን ጨምሮ ለትምህርት ቤቶች እውቅና የተሰጠ ሲሆን በ8ኛ ክፍል ክልላዊ ፈተና ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ ተማሪዎች የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቷል ።