በውጭና በሃገር ውስጥ የምትኖሩ ኢትዮጵያውያን
ውድ የከተማችን ነዋሪዎች
እንኳን አደረሳችሁ!!!
እንኳን ደስ አላችሁ፤ እንኳንም ከዘመን ዘመን አሸጋገራችሁ፤ የሚሉ ቃለት አዲስነትን ማላበስ ጉልበት አላቸው፤ ተስፋን የማጋባት ኃይል አላቸው፤ ደስታን የማጎናጸፍ አቅም አላቸው፤ እንኳንም ከዘመን ዘመን አሸጋገረን አሸጋገራችሁ፡፡
ዘመን ሰው ነው ፤ ዘመን እኔና እናንተ ነን፤በዘመን ውስጥ እኛ ነን ጎልተን መታየት ያለብን፡፡ የሚጠቀስ ተግባር፣ የሚነገር ታሪክ፣ አርአያ የሚሆን ሥራ፤ በዘመኑ ውስጥ እንድንሰራ ዘመኑ ተሰቶናል፡፡ በዘመን ስሌት መጠቀም የእኛ ፋንታ ነው፡፡ መሸጋገራችን ትርጉም እንዲኖረው ማድረግ የሁላችን ኃላፊነት ነው፡፡
ከዘመን ዘመን መሸጋገርን ጊዜ መቁጠር ብቻ አድርገን እንዳንወስደው፤ 2013 አልፎ 2014 ተተካ ብለን ስንል በእኛ ህይወት ውስጥ ስለተተካው አዲስ መንፈስ፣ ስለተተከለው ኢትዮጵያዊነት፣ ስለሰነቅነው አገልጋይነት፣ ስለቀጣይ ተግባራዊ መልካምነት፣ ከእኔ በላይ ለአገሬ ስለሚለው አኩሪ ጀግንነት፣ እነዚህን ሁሉ ቀምሮ አሸናፊነትን ስለሚያበስረው የድል ስኬት ብስራት ቀን ጭምር ማሰብ ይኖርብናል፡፡
ዘመን ማለት ይህ እሳቤ ነው፡፡ በዘመን ውስጥ የምንታየው እንዲህ አድርገን ራሳችንን ስንፈትሸው ነው፡፡ የሚቀር ሳይሆን የሚተርፍ ብዙ ስንቅ ያለን መሆኑን መቃኘት ስንችል ነው፡፡
ውድ የከተማችን ነዋሪዎች
ክቡራት እና ክቡራን
2014 ዓመተ ምህረት የሁላችን መዲና የሆነችው አዲስ አበባ የበለጠ ደምቃ እንድትታይ እድሉን አግኝተናል፡፡ አዲስ ኢትዮጵያ የድል ነጸብራቅ መሆኗን ለማስመስከር ዘመን ተጨምሮልናል፡፡ የከተማ አስተዳደሩ አዲስ አበባ እና ነዋሪዎቿን ወደብልጽግና ለማድረስ የበለጠ ተባብረን መስራት ያስፈልገናል፡፡
ለዚህ ደግሞ በጀመርነው የዘመን ድልድይ እሳቤዎች በኢትዮጵያዊነት፣ በአገልጋይነት፣ በመልካምነት፣ በጀግንነት እና በድል ቃል ኪዳን አብሳሪነት፤ አዲስ ዘመን የተቀበልንባቸው ስንቆች ናቸው፡፡ የእድሜአችን መስታወቶች ናቸው፡፡ የ2014 አዲስ ዘመን የተግባር አምዶች ናቸው፡፡
አሁን የምንገኝበት የዘመን እጥፋት ፍትህ እና ወንጀል፣ እውነት እና ሃሰት፣ ሀገር ወዳዶች እና ሀገር ጠሎች፤ ግንባር የገጠሙበት ነው፡፡ የፍትህ አገሯ ፍትሃዊያን ፣ የእውነት ቤቷ እውነተኞች፣ የአገር ወዳዶች ቦታ ኢትዮጵያ፤ መሆኗን ለማስመስከር 24/7 መትጋት ይጠበቅብናል።
አዲስ አበባ የኢትዮጵያ ድል ነጸብራቅ ናት፡፡ የአብሮነት ማማ ናት፡፡
ውድ የከተማችን ነዋሪዎች አዲስ አበባን የመስከረም አደይ ፍካት ለዛን እንደያዘች እንድትቀጥል በ2014 ዓመተ ምህረት ብዙ ውጥንና ትልም አለን፡፡
የከተማችን ነዋሪዎች በኢኮኖሚ ተጠቃሚ እንዲሆኑ፣ በሚሰጣቸው አገልግሎት እንዲረኩ፣ የከተማችን መዲናነት ማእከል ያደረጉ ፕሮጄክቶችን ከግብ ለማድረስ እንድችል፤ በጋራ መቆም አለብን፡፡
ለዚህ ደግሞ ኢትዮጵያዊነት ይንገስብን፣ ጽኑ አገልጋይነትን እንላበስ፣ መልካምነት አይለየን፣ ጀግንነት ይለምልምብን፣ የድል ብስራት ዜናን እየሰማንና እያሰማን መቀጠል አለብን፡፡ 2014 የኢትዮጵያ የትንሳኤ ዘመን ነው፤ የአዲስ አበባችን የአዲስነት ዓመት ነው፡፡ የህዝባችን የብልጽግና ዘመን ነው፡፡ እናምናለን ይሳካልናል፤ ለዚህ ደግሞ ቁርጠኝነቱ አለን፤አይቀርም እናሸንፋለን፤ የድል ሸማን ለብሰን በአሸናፊው ብርሃን ውስጥ እንመላለሳለን ፡፡
መልካም አዲስ ዓመት፡፡
ኢትዮጵያ በድል ለዘላለም ትኑር፡፡
ፈጣሪ ኢትዮጵያን ይባርክ፡፡ አመሰግናለሁ፡፡