12ኛው የአዲስ አበባ የቴክኒክ ሙያ እና ቴክኖለጂ ሳምንት አውደ ርዕይ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በተገኙበት በወዳጅነት ፓርክ ለጎብኝዎች እይታ ክፍት ተደረገ፡፡
የአዲስ አበባ ቴክንኪ ሙያ ስልጠናና ልማት ቢሮ ሙያና ቴክኖሎጂ ለምርታማነት በሚል መሪ ሃሳብ የከተማ ነዋሪዎችን የቴክኖሎጂ ፍላጎትና የልማት እንቅስቃሴ የሚደግፉ በቴክኒክ ሙያ ተቋም የተፈበረኩ አገር በቀል የፈጠራ ውጤቶች አውደ ርዕይና ኤግዚቢሽን በወዳጅነት ፓርክ ለተከታታይ ቀናት ለተጠቃሚዎች ክፍት ተደርጓል
ኢንዱስትሪ፣የፈጠራ ስራና ቴክኖሎጂን የከተማ አስተዳደራችን ለሕዝባችን የገባውን ቃል አንድ በአንድ ለመመለስ እንዲችልና ሕዝባችንን ተጠቃሚ ለማድረግ አይነተኛ ቁልፍ መሣሪያዎቻችን ናቸው ብለን አምነን ከሚመለከታቸው ሁሉ ጋር በጋራ ትኩረት ሰጥሀን እየሰራን እንገኛለን ብለዋ ከንቲባ አዳነች ።
በሀገራችን ምርት መኩራትን በአንደበት መናገር ብቻ ሳይሆን ገዝተን በመጠቀም ለሀገር በቀል ምርቶች ዕውቅና ልንሰጥና አምራቾችን ልናበረታታ ይገባል ያሉት ከንቲባ አዳነች የአገራችንን ኢኮኖሚ ከቃላት ባለፈ በተግባር የምንደግፍበትም አይነተኛ መንገድ ነው ሲሉ አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል።
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ሚንስትር ዲኤታ ዶ/ር በከር ሻሌ በበኩላቸው ክህሎት በራስ የመተማመን ምንጭ ነው ብለው በራስ መተማመን ደግሞ ለፈጠራ ስራዎች ሁሉ መክፈቻ ቁልፍ በመሆኑ ከችግሮቻችን ሁሉ በቶሎ ለመውጣት አገር በቀል የፈጠራ ሥራዎችን በሙሉ አቅማችን ልንደግፍ ይገባል ብለዋል።
ተጠቃሚዎች ለተከታታይ ቀናት ወዳጅነት ፓርክ እየመጡ ምርቶችን እንደየፍላጎቶቻቸው ገዝተው በመጠቀም አምራቾቸንና አገር በቀል ፈጠራን ማበረታታት እንዲችሉ ኤግዚቢሽንና አውደ ርዕይን መርቀው ክፍት እንዲሆን ተደርጓል።