በተለይም በከተማ አስተዳደራችን ውስጥ በመንግስት ድጎማ እየተሰራጨ ያለውን የምግብ ዘይትና ዳቦ በተመለከተ ልዩ ትኩረት ሰጥተናል።
የምግብ ዘይት በህገወጥ ክምችት የተገኘውንም ጨምሮ በተለያዩ አቅራቢዎችም እንዲቀርብ በማድረግ ለጊዜው ከ2 ሚሊዮን ሊትር በላይ ዘይት እያሰራጨን እንገኛለን፡፡
በመሆኑም የከተማችን ነዋሪ በተለይም በዝቅተኛ ገቢ የምትተዳደሩ በየአካባቢያችሁ ወደሚገኙ የሸማች ሱቆች በመሄድ ምርቶቹን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
የሸገር ዳቦን በተመለከተ ፋብሪካው በእድሳትና በወቅቱ የስንዴ ዋጋ ንረት ምክንያት ለጊዜው ማምረት አቁሞ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ይህንኑ የስንዴ አቅርቦት ችግር ለመፍታት በከተማ አስተዳደሩ ለሸገር ዳቦ 613 ሚሊዮን ብር ድጎማ በማድረግ፣ እንዲሁም በፋብሪካው 198 ሚሊዮን ብር በድምሩ 812 ሚሊዮን ብር በመመደብ የዳቦ ምርት ማስጀመር ተችሏል፡፡
ከነገ ጀምሮም ምርቱ ወደ ገበያ የሚወጣ በመሆኑ ህብረተሰቡ የሸገር ዳቦ በምናሰራጭባቸው ማዕከላት ዳቦ ማግኘት ይችላል።
ነገር ግን እነዚህ ምርቶች ዝቅተኛውንና በተለይም ቅድሚያ ወደሚሰጠው ህዝብ በሚፈለገው ደረጃ መድረስ ላይ እጥረቶች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ይህንንም ለመቅረፍ የከተማ አስተዳደሩ የጀመረው ቁጥጥር ቢኖርም ነገር ግን ህዝቡ በተለይም የዳቦ በመንግስት ከፍተኛ ድጎማ እየቀረበ ሳለ የተሻለ ገቢ ያላቸው የንግድ ድርጅቶችና ባለሃብቶች ምርቱን ወስደው የሚያተርፉበት ሁኔታ እንዳለ መረጃዎች ይጦቅማሉ ፡፡
ህብረተሰቡ ይህንን ሁኔታ በመጠቆምም፣ በማጋለጥም፣ በመቆጣጠርም በኩል ድርሻውን እንዲወጣ ጥሪዬን አቀርባለሁ።
የከተማችን የንግዱ ማህበረሰብም በመተሳሰብ ለጊዜው ትርፋችሁን ቀንሳችሁ ህዝባችሁን እንድትደግፉ ዘንድ በአክብሮት ጥሪ እናቀርብላቹሃለን
ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ