
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር
ዐቃቤ-ህግ ቢሮ
ዐቃቤ-ህግ ቢሮ
ርዕይ
በ 2022 ዓ.ም. አዲስ አበባን የሕግ የበላይነት የተረጋገጠበት ከተማ ማድረግ ነው፡፡
ተልዕኮ
ለአዲስ አበባ ከተማ ልማት እና መልካም አስተዳደር የሚያግዙ ሕጐች እንዲወጡና ንቃተ-ሕግ እንዲፈጠር በማድረግ ተደራሽ እና የተቀላጠፈ የፍትሕ አገልግሎት ለሕብረተሰቡ በመስጠት የሕግ የበላይነት እንዲረጋገጥ ማድረግ፡፡
ስልጣንና ተግባራት
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የከተማውን አስፈፃሚ አካላት እንደገና ለማቋቋምና ስልጣንና ሀላፊነታቸውን እንደገና ለመደንገግ ባወጣው አዋጅ ቁጥር 64/2011 መሰረት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ዐቃቤ-ህግ ቢሮ ሚከተሉት ስልጣንና ተግባራት አሉት፡-
- በሕግ ጉዳዮች የከተማው አስተዳደር ዋና አማካሪና ተወካይ ሆኖ ይሠራል፤
የከተማውን የፍትህ ሥርዓት ማሻሻያ ፕሮግራምን ያቅዳል፤ ያስተባብራል፤ በእቅዱ መሰረት መከናወኑን ያረጋግጣል፤ ይከታተላል፤ ክፍተቶችን እየለየ ድጋፍ ያደርጋል፤
የሰብዓዊ መብት የድርጊት መርሀ-ግብር ይተገብራል፤ አስፈፃሚ አካላት በዋና ዕቅዳቸው ማካተታቸውን ያረጋግጣል፤ ይደግፋል፤ አፈፃፀሙን ይከታተላል፤ ለሚመለከታቸው አካላት ሪፖርት ያቀርባል፤
ሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመከላከል ፕሮግራሞችን ይቀርፃል፤ በሚመለከተው አካል ሲጸድቅ ተግባራዊ ያደርጋል፤ ይመራል፤ ያስተባብራል፤ አፈጻጸሙንም ይከታተላል፤
የከተማው አስተዳደር መስሪያ ቤቶች የአስተዳደሩና የነዋሪው መብትና ጥቅም ወኪል ሆኖ ይከራከራል፣ ያስከብራል፣ የሚከበሩበትን ሂደት ይከታተላል፤ ይቆጣጠራል፤
የከተማው አስተዳደር የመንግስት መስሪያ ቤቶች የሚያደርጉትን ውል እንደአስፈላጊነቱ ይመረምራል፤ ሕጋዊነታቸውን ያረጋግጣል፤ አፈጻጸማቸውን ይከታተላል፤ ተገቢው የጥንቃቄ እርምጃ እንዲወሰድ ያደርጋል ወይም ይወስዳል፤
የከተማው አስተዳደር የመንግስት መስሪያ ቤትን እና የመንግስት ልማት ድርጅቶችን በመወከል በማንኛውም የዳኝነት ሥልጣን በተሰጠው አካል ወይም በግልግል ጉባኤ በመቅረብ ክስ ይመሰርታል፣ መልስ ይሰጣል፣ የጣልቃ ገብ፣ የመቃወም እና የይግባኝ አቤቱታ ያቀርባል፤
የከተማ አስተዳደሩን የህዝብ መብትና ጥቅም ለማስከበር አስፈላጊ ሆኖ ሲያገኘው በማንኛውም የዳኝነት ሥልጣን በተሰጠው አካል ወይም በግልግል ጉባኤ በመቅረብ በስሙ ክስ ይመሠረታል፤ መልስ ይሰጣል፤ የጣልቃ ገብ አቤቱታ ያቀርባል፤ ይግባኝ ይጠይቃል፤
የተሰጠው ውሣኔ የህዝብንና የመንግስትን ጥቅም የሚጐዳ ሆኖ ካገኘው የመቃወም አቤቱታ ያቀርባል፤ ይከራከራል፤
የአስተዳደሩ ተቋማት ከአሰሪና ሰራተኛ ጋር ተያይዘው የሚቀርቡ የክርክር ጉዳዮችን ወክሎ ይከራከራል፤ ያስወስናል፤ ያስፈጽማል፤
በከተማው አስተዳደር የመንግስት መስሪያ ቤቶች እርስ በእርሳቸው ያልተግባቡባቸው የፍትሐብሔር ጉዳዮች በፍርድ ቤት ወይም ከፍርድ ቤት ውጪ ባለ አማራጭ የክርክር መፍቻ መንገድ እንዲወሰን ውሣኔ ይሰጣል፣ በውሣኔ መሠረት መፈፀሙን ይከታተላል፤
በካቢኔው በሚፀድቅ ወይም በፀደቀ መዋቅራዊ አደረጃጀት መሠረት የራሳቸው የሕግ አገልግሎት እንዲኖራቸው የተፈቀደላቸው አካላትን የህግ አገልግሎቶች በሚመለከት ወቅታዊ ሪፖርት እንዲቀርብለት ያደርጋል፤ የጉዳይ አያያዛቸውን ወይም ስራቸውን ይከታተላል፤ ይደግፋል፤ ይቆጣጠራል፤ የማስተካከያ እርምጃ ይወስዳል፤